የኑሱክ ንይያ
እሕራም ማድረግ የፈለገ ሰው ገላውን ታጥቦ፣ንጽሕናውን አሟልቶ፣የእሕራም ልብስ ሲለብስና ወንድ ከተሰፉ ልብሶች ነጻ ሲሆን የሐጅን ወይም የዑምራን ኑሱክ ለመጀመር ንይያ ያደርጋል፡፡ ለማከናወን የነየተውን ኑሱክ በአንደበቱ ጭምር በመግለጽ ዑምራ አድርጎ ከዚያ በሐጅ ተመቱዕ ለማድረግ ከፈለገ ‹‹ለብ’በይከ አልሏሁም’መ ዑምረተን ሙተመት’ትዐን ብሃ እለል ሐጅ›› ይላል፣ወይም ‹‹ለብ’በይከ አል’ሏሁም’መ ዑምረተን›› ይላል፡፡
ሐጅ ብቻ ነይቶ ከሆነ ደግሞ ‹‹ለብ’በይከ አልሏሁም’መ ሐጀን›› ማለት የተወደደ ነው፡፡ አነስ (ረዐ) የአላህ መልእክተኛ ﷺ ‹‹ለብበይከ ዑምረተን ወሐጃ›› (አላህ ሆይ! አቤቱ ለዑምራና ለሐጅ ጥሪህን ተቀብዬ አቤት ብያለሁ›› [በቡኻሪና ሙስሊም የተዘገበ] ሲሉ ሰምቻለሁ ብለዋልና፡፡ በአንደበቱ ምንም ሳይል ቀርቶ በልቡ ብቻ ንይያ ካደረገም በቂው ነው፡፡
የኑሱክ ዓይነቶች
1 - ተመት’ቱዕ (ዑምራ ከዚያ ሐጅ)
ይህ በሐጅ ወራት ውስጥ ለዑምራ እሕራም አድርጎ ዑምራውን ከፈጸመና ከእሕራሙ ከወጣ በኋላ በዚያው ዓመት ለሐጅ እሕራም የሚያደርግበት ዓይነት ነው፡፡ በተመቱዕ ሐጅ የሚያደርግ ሰው መካ በሚደርስበት ጊዜ የዑምራ ተግባራትን ያከናውናል፡፡ እነሱም ፡- ጠዋፍ፣ሰዕይ፣ጸጉር መላጨት ወይም ማሳጠር፣ከዚያም ከእሕራሙ በመውጣት መደበኛ ልብሱን መልበስ ሲሆኑ፤የዙልሕጃ ስምንተኛ ቀን ሲደርስ ለሐጅ እሕራም አድርጎ የሐጅ ተግባራትን ማከናወን ነው፡፡ በዚህ የተመቱዕ አፈጻጸም ዓይነት የተጠቀመ ሰው ሀድይ (በመካ የሚሰዋ እንስሳ) የማረድ ግዴታ አለበት፡፡
2 - ቅራን (የሐጅና ዑምራ ጥምረት)
ይህ አፈጻጸም ለሐጅና ዑምራ በጥምረት እሕራም ማድረግ ወይም ለዑምራ እሕራም አድርጎ ጠዋፉን ከመጀመሩ በፊት ሐጅን በዑምራው ላይ ማስገባት ነው፡፡ በቅራን አፈጻጸም ዓይነት ሐጅ የሚያደርግ ሰው የሐጅ ተግባራት በሙሉ እስኪሟሉ ድረስ በእሕራሙ የሚቀጥል ሲሆን በማጣመሩ ምክንያት ሀድይ የማረድ ግዴታ ይኖርበታል፡፡
3 - እፍራድ (ሐጅን ብቻ በነጠላ)
ይህ ሐጅ ብቻ በነጠላ የሚከናወንበት የአፈጻጸም ዓይነት ሲሆን፣በዚህ የተጠቀመ ሐጅ አድራጊ እስከ መጨረሻው የሐጅ ተግበራት ፍጻሜ ድረስ በእሕራሙ ይቀጥላል፡፡ የሀድይ ግዴታም የለበትም፡፡
ከሁሉም ተመራጩ ኑሱክ (አፈጻጸም) ነቢዩ ﷺ ሶሓባን [ሙስሊም በዘገቡት የዓእሻ ሐዲስ መሰረት፡፡] በዚህ ያዘዟቸው በመሆኑ የተመቱዕ አፈጻጸም ነው፡፡ ከዚያ ቅራን ቀጥሎም እፍራድ ነው፡፡
በሦስቱ ኑሱኮች (የሐጅ ሥርዓት አፈጻጸም) መካከል ያለው ልዩነት